ይኑር ሰው ከዋሽንግተን ዲሲ
በዚያን ሰሞን በተከታታይ ሳምንት በአንዲት ትንሽ ”ቅድስት አገር” በተሰኘች ድረ ገፅ ላይ ስለ በሰሜን
ምስራቅ ዋሽንግተን ዲሲ ስለሚገኘው ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የሚያወሱ ፅሑፎችን አንብቤ ነበር።
ፅሑፎቹ የሚደንቁ ናቸው። ለረጅም ግዜ ከሕዝብ ተደብቀው የኖሩ እውነታዎችን ገሀድ አውጥተዋል።
የሚገርመው ለብዙዎቻችሁ አዲስ ቢሆኑም ለኔ ግን አዲስ አልነበሩም። የሆነ ሆኖ ይህንን ጉድ ሁሉ
ለብቻዬ መሸከሜ እጅግ በጣም ከብዶኝ በዝምታ በመተባበሬ ህሊናዬን እረፍት ነስቶኝ ነበር። ለፀሐፊው
ኃይለ ገብርኤል ታደገ ምስጋናዬ ይድረሰውና የሱን ምሳሌ በመከተል ይህችን አነስተኛ ፅሑፍ በማቅረብ
ከጭንቀቴ ተገላግያለሁ። ቃላትን ማቀናጀቱ ባይሆንልኝም ምንም ሳልጨምርና ሳልቀንስ ከእውነተኛ ስሜቴን
እንደወረደ አቅርቤላችኋለሁ። የተወላገደውን አቅንታችሁ፤ የከረረውን አላልታችሁ፤ የመረረውን
አጣፍጣችሁ ትረዱልኝ ዘንድ እማጸናችኋለሁ።
በመፅሐፈ ፋርጤማ ከምዕራፍ 1 ቁ 1 እስከ 13 ያለውን በመጥቀስ ልጀምርላችሁ፤
“ በቀድሞው የገብርኤል ሊቀ መንበር ላይ የወያኔ የጥፋት መንፈስ በላዩ ላይ አደረ። ይህ የጥፋት
መንፈስም እንዲህ አለው፦ መቋሚያህን አንሳ፤ ጎረደማዎችህንም ይዘህ አምባ ወደሚባል የቅዠት ተራራ
ውጣ። አዲሱንም ባይህ ሊቀ መንበርም ከአሽከሮቹ ጋር ሆነው ይከተሉህ። እሱ ፈጣንና ቀልጣፋ አጥፊ፤
ታዛዥ እንዲሁም ቀልማዳ ባሪያዬ ሆኖ አግኝቸዋለሁና። ሕዝብም በደጀ ሰላም እንዲሰበሰብ ጥሪ
ያስተላልፍ፤ እንዲህም ብሎ ይንገራቸው፤ የጥፋት መንፈስ ቤተክርስቲያን ውስጥ ገብታለችና ይህን
ስትፈፅሙ ግን ሌብነትን፤ ውሸትን፤ መቀላመድን፤ ገንዘባችሁ አድርጉ። ነገር ግን ተጠንቀቁ! በሚሊዮን
የሚቆጠር የወያኔ ገንዘብ በዲሲ ተረጭቷል ብላችሁ አትስበኩ። ሕዝቡም አንድም ዲናር ከኔ
እንደማይወጣ ያውቃልና። ከሁሉም በላይ ግን ስብከተ ወንጌል ከምድር ገፅ ይጥፋ! ይህ ከሁሉም በላይ
የከበረ ታዕዛዜ ነው። አባቶችን አዋርዱ ጦራቸው ቀጤማ እስኪሆን ድረስ። አፋቸውንም ለጉሙ፤ ስርዐተ
ቤተ ክርስቲያን እያሉ እንዳያሳስቱ። እግራቸውንም ኮድኩዱ፤ እንዳይወጡ፤ በአካባቢያቸው ሰውም
እንዳይገባ እንዳይወጣም። የእይታ ጨረርም ላኩባቸው፤ካሜራም ይሉታል”።
ሕዝቡም ይህን በሰማ ግዜ አጉረመረመ። “እነዚህ የምናውቃቸው የሀገር ነቀዞች የቤተ ክርስቲያን
ቅንቅኖች አይደለምን? አለ።” መለየትንም ወደደ፤ እንባውንም አፈሰሰ፤ ልቡም በሀዘን ተነካ። ቤቱም
በሀዘንና በትካዜ ተዋጠ። ከሕዝቡም መካከከል እውነቱን የተናገሩ ነበሩ። ነገር ግን በአጭበርባሪዎችና
በወሮበሎች ድምፅ ተዋጡ። ሕዝቡ ግን መልሶ ወያኔ መንፈስ ነውን? ብሎ ተዛበተ።
በሀገራችን አንድ አባባል አለ። ትንሽ ሰው ትንሽ ነው፤ አንሶ ያሳንሳል ይባላል። በዚህ ቤተክርስቲያን ባለጌ
ገነነ። ትህትናን የተላበሰ በጎ ስራና ጥሩ ስነ ምግባር አይቶ ብዕሩን ሲያነሳ ብርሃን ይታየዋል መልካም
መልካሙን ያስባል፤ያሰፍራል። ነገር ግን ክፉንና ጸያፍ ስራን ሲያስተውልና ሲመለከት ደግሞ እንደዚያው
ብዕሩን አሹሎ ይህን ክፉ ስራ ይመዘግባል። አሁን እኮ የማያቸው የተረገሙ የአንድ ወንዝ ጉዶች፤ ወገንና
ዘመድን የሚያለያዩ፤ ከተሰደዱበት ሀገር እንኳን ልምድ በመውሰድ መማር ባለመቻላቸው ያበሳጨኛል።
አለመታደል ነው፤ የሀገሬ ባላገር ሲተርት “አህያ ውርንጭላ በትንሽነቱ ይዘላል ይሮጣል ይቧርቃል ከኔ
በላይ ማን አለ ይላል። መጫን ሲጀምር ግን አህያነቱን ማረጋገጥ ይጀምራል” ይላሉ። ታዲያ እነህኝን
አጥብቃችሁ ብትጭኑልኝ ማንነታቸውን ያውቁ ነበር።
ምን ያደርጋል የወያኔ ቡችላ መሆን በኬንያ ዞሮ ኢትዮጵያ እየተገባ ቤት የሚሰራው፤ ሌንቦውን ዘልጦ
ከቅድስት እስከ መቅደስ የሚያዘጠዝጠውን፤ እኔ ብቻ ነኝ አዋቂ ብሎ የሚያናፋውን ማየትና ወያኔ
የሰጠውን የማፍረስ አደራ ለመወጣት ሌት ተቀን ያለ እረፍት ነጋ ጠባ ሳይሉ፤ በአርዕዮስ ተክሌ እየማሉ
ቤሳቢስቲን ሳያወጡ ሙሉ ጌታ ነኝ ብሎ እየተንጎራደዱ ፤ ሕዝብ ቆሞ የሰራውን ቁጭ ብለው ሲያፈርሱ
ማን አዋየ ማን መከተ? ቂሉ ወይስ ጉዱ ካሳ? ተዉኝ ጉድ እስከ ወዲያኛው ይሉ የለ! እስቲ ፍረዱኝ፤
የሕዝብን አንድነት እንደ ቅንቅን የሚበሉ ነቀርሳዎች፤ የቤተክርስቲያን ሰላምና ፍቅርን የሚነሱ፤
አዕምሯቸው የሰባ፤ የፖለቲካ አመለካከት ብቻ ይዘው እንደ ደርግና ወያኔ እኛ ብቻ እናውቅልሃለን
የሚሉ፤ ተምረው እንዳልተማሩ እያዩ የማያስተውሉ፤ እየሰሙ የደነቆሩ፤ የደነዘዙ ግኡዝ ፍጥረቶች፤
ሰውነታቸው ብቻ አሜሪካ የገባ፤ አስተሳሰባቸው ጨቅላ የሆኑ ፋራዎች ናቸው።
እስቲ ወደ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ስትገቡ በጌትነት ሲቅበዘበዙ ስታዩ፤ የቀበሌ ወይም የደርግ ጽህፈት
ቤት የተቃረባችሁ አይመስላችሁም? ወይንስ የአራዳ ዘበኞች ቁርስ ፍለጋ የሞቀ ሻይ ለመጠጣት ተራ
የሚጠብቁትን? እኔ እንጃ! አንድ ነገር ግን በቁጥር 1 ቦርድ ጽ/ቤት ሳልፍ አዲስ አበባ ድሮ በደርግ፤ ዛሬ
ደግሞበወያኔ ግዜ ያለሁ ይመስለኛል። የሰዎች ጠረን ተቀይሮ፤ አፋቸው ኩበት መስሎ የመንገድ ላይ
ተዳዳሪንም በመምሰል ያሳስታሉ። ወይንስ ለጽድቅ ሲጸልዩ አድረው ይሆን? ተምታታብኝ፤ የት እንዳለሁም
ግራ ይገባኛል። ድንገት ግን በጆሮዬ ሰይጣን ሹክ አለኝ። ”አልሰማህም? በዚህ የመሸገው የአፍ ነበልባል
ጦር አዲስ አበባ ያለውን የወያኔ የእናት ጦር እያርበደበደ ይገኛል። በማንኛውም ሰዓት ተወርውሮ
ሊመታውና ሊቀላቅለው ያስባል” ብሎ ደስ አሰኘኝ።
ለዚህ ሁሉ ብጥብጥና የቤተክርስቲያን መናጋት ዋና ምክንያት የሆነው የድሮ ሊቀ መንበር የቀበራቸው
የሰው ፈንጂዎች ናቸው። ከቦርድ አመራረጥ ጀምሮ አሁንም አሽከር የሆኑት ደብተራ ከለንደን ስራዬ ብሎ
በሚስጥር ያስመጣቸው ሊቀ ጳጳስ ናቸው። ይህ ሰው የሚታወቅበት ዋንኛ ባህሪው ቅጥፈት ነው። ጥዋት
የተናገረውን ማታ የሚክድ፤ ማታ የሰራውን ሲነጋ እኔ አይደለሁም የሚል፤ ተማርኩ ብሎ የሚኮፈስ፤ ነገር
ግን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ይዞ ማስተዳደር ያልቻለ ግብዝ ሰው ነው። ከሁሉ በላይ ግን ሁሉን ያሳዘነና
ልብ የሰበረው ካህናትን ከመቅደስ ውስጥ በፖሊስ ያባረረ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊና ሃይማኖት የሌለው
አረመኔ ሰው መሆኑ ነው። ስለዚህ ሰው ገና ያልተነገረ ብዙ ጉድ አለ። እሱን ልተውና ስለ ለንደኑ ሊቀ ጳጳስ
ላውራ። ያልታወቀባቸው የተንኮል መሀለቅ ይሏቸዋል። እንዲያውም ኩርፋፍያ የቆላ እባብ መርዙ
የማይድን ብለው ያወድሷቸዋል። እስቲ ተመልከቷቸው፤ የካህናቱን የጸሎት ልብስ እንደ ድብዳብ
በላያቸው ላይ ጭነው እንደጉርና ይገፋሉ። ስለ ክርስቶስ መምጣት ገና በተስፋ የሚጠባበቁ፤ በእድሜ
የበሰሉ፤ ስለ አዲስ ኪዳን ግን በምንም አይነት የማይታሙ፤ ወንጌል ሲነገር፤ ስለ ክርስቶስ ማዳን ሲሰበክ
የሚተናነቃቸው ናቸው። አለማወቅ ኃጢአት አይደለም። የሚያሳዝነው ግን በለንደን ተሰደው ሲኖሩ
ከአንድ ዲያቆንና ቁጥር ከማይገቡ ሰዎች ተስማምተው መኖርና መፀለይ አቅቷቸው ቤተ ክርስቲያን ተዘጋ።
አሁን በማያውቁትና ባልሰሩት ቤተ ክርስቲያን ተወዝፈው አበል እየተከፈላቸው መኖር አቅቷቸው
መበጥበጥን መረጡ። ፍትሐ ነገስት እኮ የሚለው አንድ ሊቀ ጳጳስ በሌላ ሀገረ ስብከት ሲሄድ ከሰባት ቀን
በላይ በእንግድነት መኖር አይገባውም። እኚህ አባት ( ልበላቸው ) ግን ክፍላቸው መላወሻና መተንፈሻ
እስኪያጣ ድረስ በቁሳቁስ ተሞልቶ የንግድ መደብር ይመስላል። በዚህ ቤተክርስቲያን ውስጥ ካሜራ ገባ
ብሎ ቀጣፊው ሊቀመንበር ሲደሰኩር ጉድ ፈላ አልኩኝ። ሌባና ቀማኛ ያስቀራል ብዬ ደስ ብሎኝ
አይምሰላችሁ። አንድ የማውቀው ነገር ስላለ ነው። እኒህ በኢየሩሳሌም ሳሉ ሴት መነኮሳትን አጠምቃለሁ
እያሉ የተባበሩ አሁንም በዚህ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ሴቶችን እርቃነ ስጋቸውን እያሳዩዋቸው
መጠመቅ ጀምረዋል ስላሉኝ ነው። የውስጥ አዋቂዎች እንዲህ ያለ ነገር ካሜራው እንዳያነሳ ግዝት ነው
ይሉኛል። እኔ ይህንን አላውቅም ውርድ ከራሳቸው።
አሁን ስሰማ ደግሞ የጥንቱን የጠዋቱን የቆሎ ተማሪ ስርዐት ያልረሱ ወደ ለንደን አኮፋዳቸውን ይዘው
የእንግሊዝን መንግስት በእንተ እግዝትነ ማሪያም መኖዬ ይሰፈርልኝ ይላሉ አሉ። እንዲህ ነው
ለእግዚአብሄር መንግስት ማደር። የኩሺናው ዶክተር የሲኖዶሱ ጽ/ቤት ልዩ ሃላፊ ሆነው ተሹመዋል ብሎ
ነበር። ስራ አይተጓጎልባቸውም። ዘባረቅሁ ወይስ ተማቶብኝ ነው። ቂሉ ካሳ ሆንኩ መሰለኝ።
በስደት ያለው ሲኖዶስ ፀሐፊ የሆኑት አባት ስርዐት ፈረሰ፤ ተበላሸ ፓትርያርክ በህይወት እያለ ሌላ
አይሾምም ብለው ተሰደው ራሳቸው ስርዓት አፍራሽ ሆነው ያተራምሱታል። ካልተበጠበጠ አይጠራም
የሚልም ዘይቤ አላቸው። ለምሳሌ የሲኖዶስ ድጋፍ ሰጪ ( የፖለቲካ ፓርቲ ) የአመኔታ ጉባኤ የጳጳሳትን
ስልጣን የነጠቀ ስርአተ ቤተክርስቲያንን የሚያሽመደምድ ነው። ካረጁ አይበጁ ወይስ እድሜ ዘልዛላው?
እኔ አላውቅም። ለመሆኑ የቤተክርስቲያን ሊቃውንት የወንጌል ገበሬዎች የት ሄዱና ነው?
በቤተክርስቲያን ውስጥ በክፋት የቆመ ቢኖር ይወገድ እያለ ገብረ ሰናየው ወይም ዋናው ቀዳሽ ካህን ቅዳሴ
ከተጀመረበት ዘመን ጀምሮ ይፀልያል። ታዲያ ምነው እየበዙ ሄዱ። ፀሎቱና ፀበሉ አልይዝ አልሰምር አለ
እንዴ? እያልኩ ጨንቆኝ የንስሃ አባቴን ጠየኳቸው። አዬ ልጄ አሉና ተገርመው፤ መጀመሪያ የሰይጣን ቤት
የት ሆኖ፤ መቅደስ እኮ ነው አሉኝ። እረፉት እንግዲህ! አንድ ነገር ግን ትዝ አለኝ። በቅዳሴ መሃል
አቋርጦ፤ ልብሰ ተክህኖውንም ወርውሮ የሄደው፤ በድፍረት ያለፍርሃት ከዲያቆን መነኩሴ እስከ ሊቃ ጳጳስ
ማይክሮፎን ከእጅ የሚነጥቀው፤ አባቶችንም ሕዝብንም የሚገላምጠው፤ ስጋ ወደሙ ሲፈተት
የሚክለፈለፈው፤ ለምንም ክብር የሌለው ደብተራ ለካስ ወዶ አይደለም በራሱ ላይ ሰይጣን ሰፍሮበት
ነው! እግዚኦ በሉ፤ እንዲህ ያለው ቀጣፊና ቀልማዳ የጋኔን ቤት ነገር ሰሪ ማስወጣት ነው እንጂ መዳኛም
የለው። በአውደ ምህረት በኩልም ብዙ ጉድ ታያላችሁ። ዳዊት ስለፈጣሪው እየዘለለ የክብር ልብሱን ጥሎ
ራቁቱን እስኪሆን ድረስ ዘመረ፤ እግዚአብሔርንም አመሰገነ ይለዋል። ዛሬ ደግሞ የገብርኤል መዘምራን
ምን እንደነካቸው አላውቅም እናሸንፋለን ሆኗል። አብዮት አደባባይ ያለሁ ይመሰለኛል። አንዳንድ ግዜም
የጠራ ስድብ ናዳ ሲወርድ የመሸታም የቃልቻም ይመስላል። ግራ የሚያጋባ ሆኗል።
ከበሮ እየደለቁ እንጡርብ ቢዘሉ፤ ማሲንቆ ይዘው ቢገዘግዙ ዕዳ እንደሁ ከራስ አይወርድም። የወንጌልን
ትምህርት ንቆና አቃሎ ብሎም ረግጦ በትዕቢት እንደ ግድግዳ ቆርቆሮ መጮህ አይጠቅምም። የልጆችን
ጨዋታ ልተውና የምስራች ልበላችሁ። በናፍቆት የምንጠብቀው እናንተ በሌለ ነገር ታምናላችሁ እያሉ
የሚመጻደቁት የደርግ አቀንቃኝ የነበሩት እመቤት ንስሀ ገቡ መሰል ለእኔና ቤተሰቤ መልአኩ ገብርኤል
የሰራልኝን እኔ ነኝ የማውቀው ይሉናል።ለማያውቁሽ ታጠኚ፤ አርፈው ይቀመጡ።ይልቅስ ንስሀ ገብተው
የቀረ ዘመንዎን፤ የልጅ ልጆችዎን ለበረከት እንዲበቁ ቢቀበልዎት ይጸልዩላቸው። በየስብሰባው ላይ እኔ ነኝ
ተዘራ አይበሉ። አይቀላምዱ። የዘመድ ምክር ይስሙ።
ለሁሉም እስቲ ነገሬን ልቋጭና በገብርኤል በኩል የታዘብኩትን ላልነበራችሁ ላውጋችሁ። ጊዜውንና ሰዓቱን
ጠብቆ ተዓምሩን ሠራ ማለት ይቻላል። የብዙ ሰው ሀብትና ጉልበት ፈሶበት የተሰራው ቤt ክርስቲያን
ውስጥ ጥገኛና እንደ ውጭ ሰው የሚታይበት ሆኖ የቆየው ምዕመን ብሶቱ ፈንድቶ ብሶቱን በአውደ ምህረት
ላይ ተንስቶ አሳየ። አንዳንድ እንደ ግል ሀብት የያዙት ግለሰቦች እንደሚሉት መንበሩ ተደፈረ እውነት
ተናገሩ፤ ለምን ይህን ያህል እንዲደፈር ተነሳሳ? ጳጳሳትም ሆኑ በተለይም አቡነ መልከ ጻድቅ የቦርድ
አባላትና ደጋፊዎቻቸው መመለስ የሚገባቸው ይህንን ነው። ጥያቄ ለመመለስ ራስን መጠየቅ ያስፈልጋል።
ስርዐተ ቤተክርስቲያን ማስከበር በሚገባቸው ሊቀ ጳጳስ በየግዜው ተጣሱ፤ ሹመት ያለአግባብ ለሌላ ሰው
ተሰጠ፤ የወንጌል አስተማሪው ተባረረ፤ 16 አመት በአቀኑትና በሰሩት ቤት ስርዓት ተጣሰ ቢሉ ተባረሩ፤
የ18 አመት የቤተ ክርስቲያን የአካውንት ሂሳብ በማያሳምን ምክንያት በሊቀመንበሩና በሂሳብ ሹሙ እጅ
ብቻ አካውንት ተከፍቶ ተቀመጠ፤ የቦርድ አባላት በአሻጥር እንደ ፖለቲካ በማጭበርበር ተመረጡ፤ የቤተ
ክርስቲያኑን ደንብ በሰዓታት አጣድፈው ብዙ ሰው በሚገባ ተረድቶት ሳይመጣ አለፈ። ይህም ህግ
የቤተክርስቲያንን ህግ ጨርሶ የተጋፋና የካህናትን ስልጣን የሚቀማ አመኔታ ጉባኤ ብለው አዲስ ህግ
ጣሉበት። በተለይም የድሮ ሊቀመንበር ከመቅደሳቸው ጳጳሳትንና መነኮሳትን በፖሊስና በደብዳቤ ከግብረ
አበሮቹ ጋር አባረሩ። አሁን ያለው የቦርድ አባላት ጨርሶ የሕዝብ አመኔታ ያጣ እንደፈለገው የንግድ
ድርጅት የሚመራ፤ከሁሉም በላይ ደግሞ አባላትን የማስጠንቀዊያ ደብዳቤ በመጻፍ እንዲሁም በቴሌፎን
ማስፈራራት ጀምሯል። ቤተክርስቲያን መግቢያ ላይም ምዕመንን የሚያስፈራሩና የሚገላምጡ
ተቆጣጣሪዎች አቁመዋል። ይህንን ሁሉ ግፍ ተሸክሞ ምዕመኑ በትዕግስት መቆየቱ ያስመሰግነዋል።
መንበሩን ተዳፈሩ ብለው የሚያስወሩትም መንበሩን እኮ የሚያዋርደውም ሆነ የሚያስከብረው ሕዝብ
ብቻ ስለሆነ በኃላፊነት የተቀመጡትም ስነ ምግባር ነው። እንደዚህ ከቀለሉና ማን አለብኝ የሚሉ ከሆነ
የህዝብ አመጽ መቀስቀሱ አይቀሬ ነው። ምን አጠፋን ብሎ ራስን መጠየቅ ተገቢ ነው።
ወደ ሀገራችን ልመልሳችሁና አቡን (ጳጳስ ) የረገጠውን መሬት የሚስም ልቡ በትህትናና በፍቅር የተሰበረ
ነበር። የአሁኑ ሊቀ ጳጳስ ራሳቸው አጥፍተው እናንተ ይቅርታ ጠይቁ የሚሉና ከሳንዲያጎ፤ ካሊፎርኒያ
ማባረሪያና መሻሪያ ደብዳቤ የሚልኩ ናቸው። ታዲያ እንዴት ነው እኚህ ሰው የሚከበሩት?
ሌላው ነገር ደግሞ፤ ነብሰ ገዳይ የቤተ ክርስቲያን ደወል ደውሎ ምህረት የሚሰጥበት ስፍራ ነበር። አሁን
ግን ከካህን እስከ ምዕመን የሚባረርበት ሆኗል። ታዲያ መጮህ ይነስ? ለቆ መውጣት ይነስ? እስቲ
ፍረዱ!ይህ ቤተክርስቲያን የሚከተለው የጥንቱን የጠዋቱን የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስርዓት ነውን? ሀሰት!
ዛሬ ማስቀል የያዙ የክርስቶስ አገልጋዮች ተቀምጠው ሳምሶናይት ይዘው በአባቶች የሚነግዱ ቦርድ
የሚባሉ የዘመኑ ፈሪሳውያን ናቸው። እግዚኦ በሉ! ቤተክርስቲያንን ከጥፋት መልሱ። ለልጅ ልጆቻችሁ
የማቆየት ኃላፊነት አለባችሁና።